የዐረብ ሊግ ዋና ጸሓፊ ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር ያደረገችው ስምምነት አወገዙ
በትናንትናው እለት በተደረገው የዐረብ ሊግ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች አስቸኳይ ስብሰባ ላይ፣ ኢትዮጵያና ሶማሊላንድ የተፈራረሚት የመግባባቢያ ሰነዱ፥ “በዐረብ፣ በአፍሪካውያንና በዓለም አቀፍ መርሖዎች ላይ የተቃጣ ግልጽ ጥቃት ነው፤” ሲሉ፣ የሊጉ ዋና ጸሓፊው እንደተናገሩ፣ ኤኤፍፒ ዘገበ።
ስምምነቱ፥ የአገሪቱን ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት እንደሚጥስ በሶማልያ መንግሥት የተያዘውንም አቋም፣ የዐረብ ሊግ እንደሚደግፈው ዋና ጸሐፊው ማስታወቃቸውንና ቀጣናዊ ውጥረትንም እንደፈጠረ ማመልከታቸውን ዘገባው ጠቅሷል።
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ የአረብ ሊግ መግለጫ ኢትዮጵያ በጥብቅ ተቃውሞ ተቀባይነት እንደሌለው አሳውቋል።
የአሜሪካ መንግስት ወኪል በሶማሊላንድ እና ኢትዮጵያ የተደረገው ስምምነት ላይ ይወያያል ተባለ
የአሜሪካ መንግስት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሀመር በኡጋንዳ ካምፓላ እና በአዲስ አበባ ጉብኝት እንደሚያደርጉ የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት አስታወቀ።
ማይክ ሀመር ወደ ሁለቱ ሀገራት ከጥር 8 ቀን 2016 እስከ ጥር 15 ቀን 2016 በሚያደርጉት ጉብኝት በኢትዮጵያ፣ ሶማሊያ እና ሱዳን ጉዳይ እንደሚመክሩ መስሪያ ቤቱ ጠቁሟል።
በኡጋንዳ ካምፓላ በሚካሄደው የኢጋድ አባል ሀገራት 42ኛው አስቸኳይ የመሪዎች ስብሰባ ላይ በመገኘት ከአባል ሀገራቱ መሪዎች ጋር በኢትዮጵያ እና ሶማሊያ መካከል ስለተፈጠረው ውጥረት እንዲሁም ስለ ሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት ዙሪያ እንደሚመክሩም አስታውቋል።
አሜሪካ ኢጋድ በሶማሊያ እና ኢትዮጵያ መካከል የተፈጠረውን ውጥረት በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለመፍታት የሚያደርገውን ጥረት እንደምታደንቅ ያመላከተው የመስሪያቤቱ መግለጫ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1960 የተካለለውን የሶማሊያ ሉዓላዊነት እና
የግዛት አንድነት አሜሪካ እውቅና እንደምትሰጥ በድጋሚ ማሳሰብ ትወዳለች ብሏል።
የአፍሪካ ህብረት ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ በመካከላቸው የተፈጠረውን ውጥረት እንዲያረግቡ ጠይቋል
በኢትዮጵያ እና በተገንጣይዋ ሶማሊላንድ መካከል፣ ታኅሣሥ 22 ቀን 2016 ዓ.ም. የተፈረመውን የመግባቢያ ሰነድ ተከትሎ እየተካረረ ባለው የኢትዮጵያ እና ሶማሊያ አለመግባባት ላይ፣ በትናንትናው እለት ረቡዕ የተነጋገረው የአፍሪካ ኅብረት የጸጥታው
ምክር ቤት፣ ሁለቱ መንግሥታት ስሜትን ከተሞሉ መግለጫዎች ተቆጥበው ውጥረትን እንዲያረግቡ ጠይቋል።
በተጨማሪም፣ በሁለቱ መንግሥታት መካከል ውይይትን የሚያስጀምርና ተከታታይ ሪፖርት የሚያቀርብ ልዑክ እንዲመደብ የጠየቀው የጸጥታ ምክር ቤቱ፣ የህብረቱ የአፍሪካ ቀንድ ተወካይ የኾኑትን የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦሊሴንጎ ኦባሳንጆን ጠቁሟል፡፡
ምክር ቤቱ በስብሰባው ፍጻሜ ባወጣው መግለጫ፣ በኢትዮጵያ እና “የሶማሊያ ሰሜናዊ ክልል” ሲል በገለጻት ሶማሊላንድ መካከል በተፈረመው የመግባቢያ ሰነድ፣ በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ መካከል የተፈጠረው ውጥረት በከፍተኛ ሁኔታ እንዳሳሰበው ገልጾ፣ በአካባቢው ሰላም፣ ደኅንነት እና መረጋጋት ላይ አሉታዊ ተጽእኖ ሊፈጥር እንደሚችል ስጋቱን አመልክቷል።
ደራ ወረዳ የሰላም እጦቱ እየከፋ መምጣቱ ተገለጸ
ኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ የሚደረገዉ የታጣቂዎች ውጊያና ግጭት እየከፋ መምጣቱን የአካባቢው ነዋሪዎች አስታወቁ።
የኦሮሚያና የአማራ ክልሎችን የሚያዋስነዉ የደራ ወረዳ ለተከታታይ ዓመታት በታጣቂዎች መካከል ግጭት ይደረግበታል። ነዋሪዎቹ እንደሚሉት ተደጋጋሚዉ ግጭት ሕይወት እያጠፋ፣ ሃብት ንብረታቸዉን እያወደመ እነሱንም እያፈናቀለ ነው። ግጭቱ ትናንትም
አገርሽቶ ሰዎች መገደልና መቁሰላቸዉን ነዋሪዎቹ አስታውቀዋል።
የኦሮሚያና የአማራ ክልሎች ባለሥልጣናት ግን እስካሁን ስለ ግጭቱ ያሉት ነገር የለም።
በትግራይ የህጻናት ሞት በአራት እጥፍ መጨመሩ ተገለጸ
ትግራይ ክልል የጤና ስርዓት በመፍረሱ በሕክምና እጦትየሚሞቱትና በምግብ እጥረት የሚሰቃዩት እናቶች እና ህፃናት ቁጥር እየጨመረ መሆኑ ተነገረ ። የትግራይ ጤና ቢሮ እንደሚለው በክልሉ ከሚገኙ እርጉዝና የሚያጠቡ እናቶች መካከል 61 በመቶዎቹ
ለምግብ እጥረት ተጋልጠዋል። የህፃናት ሞትም ከጊዜ ወደጊዜ እጨመረ ነዉ።
ቢሮዉ እንደሚለዉ በትግራይ ክልል ለሁለት ዓመት በተደረገዉ ጦርነት በክልሉ ከሚገኙ የጤና ተቋማት 80 በመቶ ያክሉ ወድመዋል ወይም ተጎድተዋል። በመሆኑም ለዓመታት በተሰሩ ተግባራት ተቀይሮ የነበረው የእናቶች እና ጨቅላ ህፃናት ጤና ወደኃላ ተመልሷል። በተለይም በትግራይ የህፃናት ሞት በአራት እጥፍ መጨመሩ የክልሉ ጤ ቢሮ መረጃ ያመለክታል።
ተመድ በኢትዮጵያ ያለው ሰብዓዊ ቀወስ እየተባባሰ ነው አለ
በሰሜን ኢትዮጵያ በድርቅ በተጠቁ ክልሎች፤ ማለትም፣ በአፋር አማራ እና ትግራይ እንዲሁም በኦሮሚያ ክልል ያለው የሰብዓዊ ሁኔታ እንዳሳሰበው የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ አስታውቋል።
የተመድ ቃል አቀባይ የሆኑት ስቴፋን ዱጃሪክ በሰጡት መግለጫ፣ ድርቁ በመባባሱ ምክንያት በተጠቀሱት ክልሎች ለሚገኙ 4 ሚሊዮን ለሚሆኑ ሰዎች የሚሰጠው ምላሽ መጠናከር እንዳለበት ተናግረዋል።
በርካታ እና ተደራራቢ ቀውሶች፣ ሰዎች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚመጡ ችግሮችን መቋቋም እንዳይችሉ ማድረጉን የጠቀሱት ቃል አቀባዩ፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ለከፋ ሁኔታ ተጋላጭ እንዲሆኑ አድርጓል ብለዋል።
ከፍተኛ የገንዘብ እጥረት ባለበት እንዲሁም በአማራ እና በኦሮሚያ ክልል ግጭቶች ባሉበትም ሁኔታ ቢሆን፣ ተመድ እና አጋሮቹ የመንግስትን ጥረት በመደገፍ ላይ መሆናቸውን ቃል አቀባዩ ገልጸዋል።
ባለፈው የፈረንጆች ዓመት 12 ሚሊዮን ለሚሆኑ ሰዎች ተመድ እና አጋሮቹ ርዳታ መለገሳቸውንና 4 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው ለታቀደው ሰብዓዊ ሥራ፣ ሊገኝ የተቻለው ገንዘብ ግን አንድ ሶሶተኛ የሚሆነው ብቻ እንደሆነም ጨምረው አመልክተዋል።
Support Reyot Media:
Go Fund Me: https://gofund.me/afe7b8cb
Patreon: https://www.patreon.com/reyot/about
Follow us:
Twitter: @reyotmedia
Facebook: @ReyotMedia
Instagram: @reyot_media
TikTok: @reyotofficial
Threads: @reyot_media