የትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር አመራሮች እና የህወሓት ከፍተኛ አባላት ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ጋር ተገናኙ
ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ እና የህወሓት ሊቀመንበር ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ከፕሪቶሪያው ስምምነት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ፊት ለፊት እንደተገናኙ ተዘገበ፡፡
ይህ በፌደራል እና የትግራይ ክልል ኃላፊዎች መካከል የሚደረገው ስብሰባ በመልሶ ግንባታ እና በፕሪቶሪያ ስምምነት አፈጻጸም ላይ ያተኩራል ተብሏል።
ምክር ቤቱ በስድስት ወራት ብቻ 15 አዋጆችን ማጽደቁ ተሰማ
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባለፉት ስድስት ወራት ከቀርቡለት 23 ረቂቅ አዋጆች ውሰጥ አንድ ደንብን ጨምሮ 15 አዋጆችን ማጽደቁን የምክር ቤቱ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ዶክተር ምስራቅ መኮንን የምክር ቤቱን የስድስት ወራት ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ገለጹ።
ምክር ቤቱ ባለፉት ስድስት ወራት ከ474 የምርጫ ክልሎች ውስጥ በ305 ምርጫ ክልሎች ተመራጮች ከመረጣቸው ህዝብ ጋር ውይይት አድርገዋል ያለው የምክር ቤቱ መረጃ በተደረገው የመራጭ ተመራጭ ውይይት 1733 የሚሆኑ ጥያቄዎች ከህዝቡ መሰብሰባቸውን፤ ለ48 ተቋማት ጥያቄዎቹ ተልከው 47ቱ ተቋማት ምላሽ መስጠታቸውን አስታውቋል።
በተጨማሪም የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም እንዲሁም የግል ዳታ ጥበቃ ረቂቅ አዋጆችን ጨምሮ ሌሎች አዋጆች በቀጣይ ስድስት ወራት ምክር ቤቱ መክሮባቸው የሚጸድቁ መሆናቸውንም ተገልጿል።
አሜሪካ በመርአዊ የተፈጸመው የንጹሃን ግድያ እጅግ እንዳሳሰባት ገለጸች
በአማራ ክልል በሰሜን ጎጃም ዞን በመርአዊ ከተማ በንጹሃን ላይ የተፈጸመው ግድያ እንዳሳሰበው በመግለጽ ሁኔታው በገለልተኛ ወገን እንዲጣራ የአሜሪካን መንግስት ጠይቋል።
በኢትዮጵያ የአሜሪካን አምባሳደር በሆኑት ኤርቪን ማሲንጋ ባወጡት መግለጫ “ባልተገደበ ሁኔታ ገለልተኛ የሰብአዊ መብት ተቋማት ቦታውን እንዲጎበኙ እና ወንጀለኞችን በህግ ተጠያቂ ለማድረግ ገለልተኛ ምርመራ እንዲካሄድ” ጠይቀዋል።
አምባሳደሩ በመግለጫቸው በኦሮምያ እና በአማራ ክልሎች በመንግስት እና በታጣቂ ሀይሎች ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየፈጸመ መሆኑን የሚያሳዩ አሳሳቢ የሆኑ ሪፖርቶች እየወጡ እንደሚገኙ በመጠቆም ብቸኛው መንገድ ድርድር ማካሄድ ነው
ሲሉ አሳስበዋል።
መንግስት በሽብር ወንጀል የከሰሳቸው ተከሳሾች ላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ አስተላለፈ
የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት፣ የሥር ፍርድ ቤት በእነ ወንድወሰን አሠፋ መዝገብ በሽብር ወንጀል የተከሰሱ ተከሳሾች ክስ እንዲቋረጥ የወሰነውን ውሳኔ ትናንት ሽሯል።
ችሎት ባለመቅረባቸው ክሳቸው እንዲቋረጥ የተወሰነላቸው ምሬ ወዳጆን ጨምሮ 27 ተከሳሾች ናቸው። የሥር ፍርድ ቤቱ ክሱ እንዲቋረጥ የወሰነው፣ ተከሳሾቹ ጫካ ስለመግባታቸው ፖሊስ ባቀረበለት ማስረጃ ላይ ተንተርሶ ነበር።
መንግሥትን በኃይል የመገልበጥ ክስ ከተመሠረተባቸው 50 ተከሳሾች መካከል፣ 23ቱ በእስር ላይ ሆነው የፍርድ ሂደታቸውን በመከታተል ላይ ይገኛሉ።
በትግራይ በከፍተኛ የምግብ እጥረት የተጠቁ ህፃናት እና እናቶች ቁጥር መጨመሩን የትግራይ ጤና ምርምር ኢንስቲትዩት አስታወቀ
የትግራይ ጤና ምርምር ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ዶ/ር ሃየሎም ካህሳይ ደም አፋሳሹ ጦርነት ቢያከትምም በክልሉ ያለው የእናቶች እና የህጻናት የምግብ እጥረት መሻሻል እንዳላሰየ ገለጹ።
የዓለም ጤና ድርጅት በአንድ አካባቢ ያለው ከባድ እና መካከለኛ የተመጣጠነ የምግብ እጥረት በመለኪያው መሠረት ከ15 በመቶ በታች መሆን እንደሚገባው ቢደነግግም በትግራይ ግን ከ37 በመቶ በላይ መድረሱን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
በሰባት ወረዳዎች በተደረገ ቅኝት በተለይም ከ6 ወር እስከ 59 ወር ወይም 5 ዓመት የሆናቸውን ህጻናትን እንደተመለከቱ እና ከመካከላቸው 8.3 በመቶ የሚሆኑት ለአስገዳጅ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት የተጋለጡ መሆናቸውን ዳይሬክተሩ አስረድተዋል።
በአንድ በጎ አድራጎት ድርጅት ውስጥ የሠሩ እና ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የህክምና ባለሙያ፣ በትግራይ በእናቶች እና ህጻናት ላይ እየታየ ያለውን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት “አሳሳቢ” ሲሉ ገልጸውታል። በተለያዩ አካባቢዎች በመንቀሳቀስ ጥናት እና እርዳታ እንዳደረጉ የሚገልጹት ባለሙያው በተለይም በክልሉ በማዕከላዊ ዞን ሁኔታው የከፋ መሆኑን ይናገራሉ።
አደጋውን ለመከላከል የሚደረግ ጥረት በቂ እንዳልሆነ በማመልከትም፣ ለህጻናት በሚቀርበው አልሚ (ገንቢ) ምግብ ላይ እጥረት እና መቆራረጥ እንዳለ ገልጸዋል።
Support Reyot Media:
Go Fund Me: https://gofund.me/afe7b8cb
Patreon: https://www.patreon.com/reyot/about
Follow us:
Twitter: @reyotmedia
Facebook: @ReyotMedia
Instagram: @reyot_media
TikTok: @reyotofficial
Threads: @reyot_media