ብልጽግና ሐሰተኛ ዘመቻ ለመቆጣጠር አዳዲስ ህጎች አወጣለሁ አለ
የፀጥታ ተቋማት ለማጠናከርና ከሐሰተኛ ዘመቻዎች ለመከላከል አዳዲስ ህጎች እንዲዘጋጁ እያደረገ መሆኑን ብልጽግና ፓርቲ አስታውቋል፡፡
የፓርቲው ስራ አስፈፃሚና ማዕከላዊ ኮሚቴ ባካሄደው ጉባዔ ለፀጥታ ችግሮች ምክንያት ናቸው ተብለው በተነሱ ጉዳዮች ላይ ውይይት ተደርጓል የተባለ ሲሆን
“ጽንፈኛ ቡድኖች የሀገሪቱ የመጨረሻው የሰላም ማስጠበቂያ ምሽግ የሆኑ ተቋማትንና አመራሮችን መልካም ስም በማጉደፍ ሥራ ተጠምደዋል” ሲሉ የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የፓርቲው ሥራ አስፈጻ ኮሚቴ አባል ተመስገን ጥሩነህ መናገራቸው ተዘግቧል።
የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚና ማዕከላዊ ኮሚቴ ባካሄደው ጉባዔ በሰላምና ደኅንነት ላይ መምከሩን እና በውይይቱም በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች “ሰላማዊ እንቅስቃሴ መኖሩና “በአንዳንድ አካባቢዎች ደግሞ የጸጥታ ችግር መስተዋሉ” ተነስቷል ተብሏል።
በእስር ላይ የነበሩ የምክር ቤት አባላትና ጋዜጠኛ ወደ አዲስ አበባ እንደተዛወሩ ተሰማ
በአማራ ክልል በተከሰተው የፀጥታ ችግር ምክንያት ከታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር ውለው አዋሽ አርባ ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ ለወራት ከቆዩት ታሳሪዎች መካከል፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ አቶ ክርስቲያን ታደለ እና
የአማራ ክልል ምክር ቤት አባል አቶ ዮሐንስ ቧያለው ወደ አዲስ አበባ መዘዋወራቸውን ተዘግቧል፡፡
በተጨማሪም የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባሉ ካሳ ተሻገር እንዲሁም ጋዜጠኛ በቃሉ አላምረውም በተመሳሳይ ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ አዲስ አበባ መዘዋወራቸውን ቤተሰቦቻቸው ተናግረዋል፡፡
ስድስት ወራት ሊሞላው የተቃረበውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ የታሰሩት አቶ ክርስቲያን እና አቶ ዮሐንስ በአዲስ አበባ ሜክሲኮ አካባቢ ወደሚገኘው የፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ የተዘዋወሩት ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ነው፡፡ በአሁን ወቅት ፖለቲከኞቹ በምን ምክንያት ወደ አዲስ አበባ እንዲዘዋወሩ እንደተደረገ እስካሁን ድረስ እንዳልተገለጸላቸው ምንጮቹ ገልጸዋል።
የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች የወጪ መጋራት ክፍያ በአግባቡ እየተሰበሰበ እንዳልሆነ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ
የተማሪዎችን የወጪ መጋራት ክፍያን በወቅቱ ተከታትለው የሚያስፈጽሙ ተቋማት ቢኖሩም በርካታ የመንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት በተዘረጋው የአሠራር ሥርዓት መሠረት ክፍያውን ተከታትለው በማስፈጸም ረገድ ክፍተት እንደሚታይባቸው በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ ሰለሞን አብረሃ ገልጸዋል።
በመሆኑም የመንግሥት ገንዘብ በአግባቡ ተሰብስቦ ለተመሳሳይ ዓላማ ጥቅም ላይ እንዲውል ተቋማትና ባለድርሻ አካላት በቅንጅትና በትኩረት ሊሠሩ እንደሚገባ ሃላፊው አሳስበዋል፡፡
በከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የአስተዳደር ጉዳዮች ዴስክ ኃላፊ አቶ አብዶ ናስር በበኩላቸው የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች የወጪ መጋራት ክፍያ መከፈል በሚገባው ወቅት አለመከፈሉ የመንግስትን ተጨማሪ የኢንቨስትመንት አቅም የሚገድብ
መሆኑን ጠቅሰው ተማሪዎችም የተጋሩትን ወጪ በሚጠበቅባቸው ወቅት ካልከፈሉ ለተጨማሪ የወለድ ክፍያም ሆነ ተሰብሳቢ እዳ የሚጋለጡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
አቶ አብዶ አክለውም ይህንን ችግር ከመሰረቱ ለመቅረፍ ትምህርት ሚኒስቴር በአሰራር፣ በመረጃ ጥራትና በክትትል ረገድ ያሉ ክፍተቶችን ለመሙላት በትኩረት እየሠራ መሆኑን ጠቅሰው ጉዳዩ የሚመለከታቸው የባለድርሻ አካላትም የበኩላቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል፡፡
መንግስት ከኦሮሚያ ነጻነት ሰራዊት ድርድር ለመቀጠል ዝግጁ ነኝ አለ
በኢትዮጵያ መንግሥትና በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት መካከል ተጀምሮ ያለ ስምምነት የተቋጨውን የሰላም ንግግር ለመቀጠል መንግሥት ዝግጁ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል
ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ፡፡
በሳምንቱ መጨረሻ በብሔራዊው የኢትዮጵያ ቴሌቬዢን ጣቢያ ቀርበው በኦሮሚያ ክልል ስላለው የጸጥታው መደፍረስ እና እልባቱን በተመለከተ ማብራሪያ የሰጡት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ፤ ከዚህ ቀደም በታንዛኒያ በመንግሥት እና በኦሮሞ
ነጻነት ሰራዊት መካከል ተጀምሮ ያለ ስምምነት የተጠናቀቀውን የሰላም ንግግር ለመቀጠል በመንግሥት በኩል አሁንም ዝግጁነት መኖሩን አስረድተዋል።
በትግራይ ከ 4 ሺህ ተማሪዎች በላይ በረሀብ ምክንያት ትምህርታቸውን ማቋረጣቸው ተሰማ
በትግራይ ክልል የተከሰተውን ረሃብ ተከትሎ በተለይ ህፃናት ለከፋ ችግር ተጋልጠው እንደሚገኙ ተገለፀ። በክልሉ በረሃብ በተጠቁ አካባቢዎች የምግብ እጥረት ችግር ገጥሞአቸው ወደ ሆስፒታል የሚገቡ ህፃናት መጠን በሶስት እጥፍ ማደጉም ተነግሯል።
በምግብ እጥረት ምክንያት ትምህርት የሚያቋርጡ ህፃናት መጠን መጨመሩም የተገለጸ ሲሆን በከተሞች በልመና የተሰማሩ፣ ለጉልበት ብዝበዛ የተዳረጉ፣ ወደ ስደት የሚያመሩ በርካቶች ናቸው።
የአበርገለ የጭላ ወረዳ ትምህርት ፅሕፈት ቤት ሐላፊ መምህር ግዚያዊ ተክላይ በአካባቢው ብቻ ከ4 ሺህ በላይ ተማሪዎች በድርቁ ምክንያት ትምህርት አቋርጠዋል ይላሉ። መምህር ግዚያዊ እንዳሉት፤
ሳይመዘገብ የቀረ እንዲሁም ተመዝግቦ ያቋረጠ ጨምሮ በአጠቃላይ 4449 ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ርቀዋል። ለዚህ ዋነኛ ምክንያት ድርቅና ረሃቡ ነው። ህፃናት መማር ሲገባቸው ትምህርት አቋርጠው ልመና ላይ ተሰማርተው ይታያሉ።
የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር የኤሌክትሪክ አውቶሞቢሎች ብቻ ወደ አገር እንደሚገቡ አስታወቀ
የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አለሙ ሰሜ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው የመስሪያ ቤታቸውን የ6 ወር አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ማንኛውም የቤት አውቶሞቢል የኤሌክትሪክ ካልሆነ ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገባ መንግስት ውሳኔ ማስተላለፉን አሳውቀዋል።
የኤሌክትሪክ አውቶሞቢሎች በዓለም ላይ በስፋት እየተመረቱ መሆኑን የተናገሩት ሚኒስትሩ፥ “በኤሌክትሪክ የሚሰሩ የቤት አውቶሞቢሎች በከተማ አካባቢ ስለሚንቀሳቀሱ እና ለእነሱም የቻርጅ ማድረጊያ መሰረተ ልማቶችን በቀላሉ ማዳረስ ስለሚቻል ተመራጭ ናቸው” ብለዋል። በመሆኑም ተቋማቸው ከኤሌክትሪክ ውጪ በነዳጅ ለሚሰራ አዲስ የቤት አውቶሞቢል አገልግሎት እንደማይሰጥ ተናግረዋል።
Support Reyot Media:
Go Fund Me: https://gofund.me/afe7b8cb
Patreon: https://www.patreon.com/reyot/about
Follow us:
Twitter: @reyotmedia
Facebook: @ReyotMedia
Instagram: @reyot_media
TikTok: @reyotofficial
Threads: @reyot_media